Sidama Hawassa
+251-462-12-6495
dagoomuf@sidaamaphi.org

የጤናውን ሴክተር አንድ እርምጃ ወደፊት ሊያራምደው የሚችል ለበሽታ ቅኝትና ምርምር አገልግሎት የሚውል የተቀናጀ የተላላፊ በሽታ ተዋስያን የዘረ-መል ምርመራ እና ባዮኢንፎርማቲክስ ፕሮግራም ስራ ሊጀመር መሆኑ ተገለጸ፡፡

—————————

ክቡር ዶ/ር አየለ ተሾመ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ በዛሬው እለት በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የስብሰባ አዳራሽ በመገኘት በፕሮግራሙ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ይህ ለጤናው ሴክተር ትልቅ እገዛ ሊያደርግ የሚችለው ፕሮግራም መጀመርና የክፍሉ መቋቋም በሀገር አቀፍ ደረጃ የማሕበረሰብ ጤና እርምጃዎች መረጃን ለማመንጨት እና ለመተንተን ብሎም ለመተርጎም፣ ለመጠቀም እና ለማጋራት እንደሚያስችል አስረድተዋል።

ክቡር የጤና ሚኒስትር ዴኤታው አያይዘውም ማዕከሉ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሀብት፣ የመሳሪያ እና የሰው ሃይል በብቃት ለመጠቀም ብሎም በየደረጃው ጠንካራ ቴክኒካል አቅምን ለማዳበርና ወጪን ለመቆጠብ ብሎም ሀገራዊ ፓቶሎጂ ጂኖሚክስ ክትትልና ምርምር ለማድረግ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።

ዶ/ር መሳይ ሀይሉ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር ኢንስቲትዩቱ የፓቶጂን ጂኖሚክስ እና ባዮኢንፎርማቲክስ የልቀት ማዕከል መሆኑን አብራርተው በቀጣይ የፓቶጂን ጂኖሚክስ ክትትል ስርዓትን የመዘርጋት፣ የጂኖሚክስ እውቀትን የማመንጨት ልዩ ልዩ ስራዎች እንደሚከናወኑ አመላክተዋል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘውም ለስራው መጀመር አስተዋጾ ላበረከቱት ለጤና ሚኒስቴር፣ ለአርማወር ሀንሰን የምርምር ተቋም፣ ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና ድጋፍ ላደረጉ ለሀገር ውስጥ እና አለም አቀፍ አጋር ተቋማት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከሚያከናውናቸው በርካታ ተግባራት መካከል በኢትዮጵያ ውስጥ በሽታ አምጪ ተውሳኮችን የመከላከል አቅምን ማሳደግና ማስቀጠል እንዲሁም ከአለም አቀፍ እና ክልላዊ ተነሳሽነት ጋር በተገናኘ በህብረተሰብ ጤና ስጋቶች ላይ አስተማማኝ፣ ጥራት እና ወቅታዊ መረጃዎችን በማቅረብ የወረርሽኝ መከላከል፣ ዝግጁነት እና ምላሽ የመስጠት ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል፡፡

በእለቱ ለበሽታ ቅኝት እና ለምርምር አገልግሎት የሚውል የተቀናጀ የተላላፊ በሽታ ተዋስያን የዘረመል ምርመራ እና ባዮኢንፎርማቲክስ ስትራቴጂ ይፋ ማድረጊያ አውደ ጥናት የተካሄደ ሲሆን በመድረኩ የተለያዩ በፓቶጂን ጂኖሚክስ ዙሪያ ትኩረታቸውን ያደረጉ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ሙያዊ ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን፤ የፓቶጂን ጂኖሚክስ ተቋሙ ጉብኝትም ተካሂዷል፡፡

WWW.EPHI.GOV.ET

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *