Sidama Hawassa
+251-462-12-6495
dagoomuf@sidaamaphi.org

ጠንካራ የሕብረተሰብ ጤና አደጋ ምላሽ ለማይበገር የጤና ስርዓት ግንባታ’ በሚል መሪ ቃል የጤናው ዘርፍ ከፍተኛ የመንግሰት ኃላፊዎች እና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ኃላፊዎች የተሳተፉበት የንቅናቄ መድረክ በጅግጅጋ ከተማ ተካሄደ።

የሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳደር የተከበሩ አቶ መስጠፌ ሙሐመድ ተሳታፊዎችን እንኳን ደህና መጣችሁ ካሉ በኋላ በክልሉ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ምላሽ ከሁሉም በላይ ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ተግባራት አንዱ እንደሆነ ጠቁመዋል።

የጤና ሚኒስቴር ሚንስትር የተከበሩ ዶ/ር መቅደስ ዳባ የተከስቱትን እና ሊከሰቱ የሚችሉ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በየደረጃዉ የምትገኙ ሚኒስትሮች ፣ ሚኒስቴር ድኤታዎች ፣ የክልል ፕሬዘንዳቶች ፣ የጤና ቢሮ ሃላፊዎች ፣ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዳይሬክተሮች እና የግብረ-ሰናይ ድርጅቶች አመራሮች በቅንጅትና በትብብር መስራት እጅግ አስፈላጊና ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ መሆኑን ገልፀዋል።

አክለውም ሚኒሰቴሯ የጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በአጭር ጊዜ አሁን የተከሰቱትን የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች እና ወረርሺኞች ለመቆጣጠር የአጭር ጊዜ እቅድ አውጥቶ በዘመቻ መልክ ለመሥራት ቅድመ ዝግጅቱን አጠናቋል ብለዋል። ይህንንም እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ በትብብር ለመከወን የሁላችሁንም አስተዋፅዖ እንድታበረክቱ እያሳሰብኩ ለወደፊቱም ለምንገነባው የማይበገር የጤና ሥርዓት የሕብረተሰብ ጤና አደጋ ቁጥጥር ሥርዓት ትልቅ አስተዋፅዖ ስላለው የበኩላችሁን ድጋፍ እና እገዛ እንድታደርጉ ከአደራ ጭምር አሳስባለሁ ሲሉ ተናግረዋል።

በመድረኩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር መሳይ ኃይሉ በበኩላቸው ባለፉት ጥቂት ዓመታት በኢትዮዽያ የተከሰቱ የተለያዩ ሰዉ ሰራሽ እና የተፈጥሮ አደጋዎች ለተለያዩ ተላላፊ በሽታዎች መከሰት እንዲሁም አጣዳፊ የምግቦች እጥረት መከሰት ምክንያት ሆነዋል። ”ይህ የንቅናቄ መድረክ እንደ አከባቢው ተጨባጭ ሁኔታ ያሉ ተግዳሮቶችን በሰፊው በመወያየት በከፍተኛ አመራሩ በሚሰጠው አቅጣጫ መሠረት በአጭር ጊዜ ውስጥ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎችን ለመቆጣጠር እና ለመከላከል ይበልጥ በጋራ እና በተጠናከረ መልኩ እንድንሰራ አስተዋፅዖ ይኖረዋል፣’ ‘ በማለት ዶ/ር መሳይ ተናግረዋል።

በተመሳሳይ ዶ/ር መልካሙ አብቴ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ከማስተላለፋቸው በተጨማሪ በኢትዮዽያ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ያለበትን ነባራዊ ሁኔታ ጠቅለል ባለ መልኩ አቅርበው ወደፊት ምን መደረግ እንዳለበትና በጋራ እንዴት መሥራት እንደሚገባ ጠቁመዋል።

በንቅናቄ መድረኩ በተላለፉ መልዕክቶች መሠረት የኮሌራ ወረርሽኝ በነሐሴ 21ቀን 2014ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ሃረና ቡሉኮ ወረዳ ተከስቶ ሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎችን አዳርሷል ።በሽታዉ ከተከሰተበት ወቅት ጀምሮ እስከ አሁን በአጠቃላይ 342 ወረዳዎችን ያዳረሰ ሲሆን ከእነዚህ መካከል በ255 ወረዳዎች ላይ በሽታዉን መቆጣጠር ተችሏል። በአሁኑ ሰዓት አጠቃላይ በ9 ክልሎች ውስጥ በሚገኙ 87 ወረዳዎች ላይ በሽታዉ በወረርሽኝ መልክ እንደቀጠለ ይገኛል።

የኩፍኝ በሽታን በተመለከተ ወረርሺኙ ከተከሰተበት ነሀሴ 06/2015 ዓ.ም እስከ ሚያዚያ 13/2016 ዓ.ም 66,625 የኩፍኝ ታማሚዎች ሪፖርት የተደረገ ሲሆን፣በአሁኑ ሰዓት በሽታዉ በ8 ክልሎች ውስጥ በሚገኙ በ101 ወረዳዎች በወረርሽኝ መልክ እንደቀጠለ ይገኛል።

የወባ በሽታን በተመለከተ በሽታዉ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ክልል እና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎች በወረርሽኝ መልክ በሚባል ደረጃ የተከሰተ ሲሆን ፣ በሽታዉ በሃገር አቀፍ ደረጃ ከጥር 1/2016 ዓ.ም እስከ ሚያዚያ 13/2016 ዓ.ም ድረስ የታማሚዎች ቁጥርም 1,347,948 መሆኑን የቅኝት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ካለፉት 5 ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ከተለመደው በተለየ ሁኔታ ከፍ ብሎ እንደነበር የቅኝት መረጃዎች ያመለክታሉ።

በመጨረሻም የፓናል እና አጠቃላይ ውይይት ተደርጎ ለወደፊት ትግበራ የሚረዱ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ እና ትግበራውን ለማሳካት ቃል በመግባት መድረኩ ተጠናቋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *